ጎንደር ሕብረት በጠለምት የ100 ኩንታል..።
- gyisma83
- Dec 31, 2023
- 1 min read
በዝናብ እጥረት ምክንያት በድርቅ ለተጎዱ የጠለምት አርሶ አደሮች 100 ኩንታል በቆሎ ድጋፍ ማድረጉን የጎንደር ኅበረት ገለጸ።
ደባርቅ ፡ ጥቅምት -19/2016 ዓ.ም (ሰሜን ጎንደር ኮሙዩኒኬሽን)
"ለወገን ደራሽ ወገን ነው" በሚል መሪ ቃል የጎንደር ኅብረት ለኢትዮጵያ አንድነት የበጎ አድራጎት ማኅበር በዝናብ እጥረት ምክንያት በድርቅ ለተጎዱ የሰሜን ጎንደር ዞን አርሶ አደሮች በተለይም ለጠለምት ወረዳ ከ4 መቶ ሺህ ብር በላይ የሚገመት 100 ኩንታል በቆሎ ድጋፍ አድርጓል። ማኅበሩ ከተቋቋመለት ዓላማ አንጻር ሰው ሰራሽና የተፈጥሮ አደጋ ሲከሰት ፈጥኖ መድረስ ነው ያሉት የጎንደር ኅብረት ለኢትዮጵያ አንድነት የበጎ አድራጎት ማኅበር የኢትዮጵያ ቅርንጫፍ ፕሬዚዳንት አምላኩ ነጋሽ በዝናብ እጥረት ምክንያት በድርቅ ለተጎዱ የሰሜን ጎንደር ዞን አርሶ አደሮች በተለይም ለጠለምት ወረዳ ከ4 መቶ ሺህ ብር በላይ የሚገመት 100 ኩንታል በቆሎ ድጋፍ ማድረጋቸውን ተናግረዋል። ከዚህ በፊት የስሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ቃጠሎ በደረሰበት ወቅት የገንዘብ ድጋፍ፣ ለሁለተኛ ደረጃ ት/ቤቶች የኳስ ድጋፍ፣ በሰሜኑ ጦርነት በነበረው የህልውና ዘመቻ ለመከላከያ ሠራዊትና ለሚሊሻ ከ5 ጊዜ በላይ የተለያዩ የሎጀስቲክ ድጋፎችን እንዳደረጉም አንስተዋል። ከጠለምት ድጋፍ መልስም ለጃናሞራ ወይም ለበየዳ ድጋፍ እንደሚያደርጉ አክለዋል። "ለወገን ደራሽ ወገን ነው" በማለት ሌሎችም በድርቅ ለተጎዳው የሰሜን ጎንደር ሕዝብ ፈጥነው እንዲደርሱና የድጋፍ እጃቸውን እንዲዘረጉም አስተያየት ተሰጥተዋል። የጎንደር ኅብረት ለኢትዮጵያ አንድነት የበጎ አድራጎት ማኅበር የኢትዮጵያ ቅርንጫፍ የቁጥጥር ኮሚቴ አባል የኾኑት ደሱ አስማረ ወገን በረኀብ ሲጎዳ ማየት የሚያንገበግበው ይህ በጎ አድራጊ ማኀበር በዞኑ በድርቅ ለተጎዱ ወረዳዎች በሚችለው መጠን ለመደገፍ እየተንቀሳቀሰ ነው ብለዋል። በዝናብ እጥረትም ኾነ ወቅቱን ባልጠበቀ ዝናብ በዞኑ አርሶ አደሮች ላይ ያስከተለውን ድርቅና ረኀብ ግምት ውስጥ በማስገባት "ሰው መኾን በቂ ነው" በሚል መርህ የሁሉንም ዜጋ የድጋፍ እጅ መዘርጋት እንደሚያስፈልግ አስገንዝበዋል።
ዘገባው፦ በእሸቴ አቡሐይ
Comments